16/04/2026
አምባ ሐዋዝ የበገና ቤተ መዘክር እና ትምህርት ቤት ተመርቆ ተከፈተ!
ሚያዚያ 8፣ 2018
ክርስቶስ ተንሥኣ እሙታን
በአቢይ ኃይል ወሥልጣን
አሰሮ ለሰይጣን
አግአዞ ለአዳም
ሰላም
እምይእዜሰ
ኮነ
ፍስሐ ወሰላም
አምባ ሐዋዝ የበገና ቤተ መዘክር እና ትምህርት ቤት ተመርቆ ተከፈተ። ያለፈውን አሁን ያለውን እና ወደፊት የሚመጣውን በገነኛ ትውልድ ለማስተሳሠር ታልሞ የተሰናደው ይህ አምባ የተከፈተው ሚያዚያ 6 በቅዱስ ዳዊት ዓመታዊ በዓለ ልደት ላይ ነበር። በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ ታላላቅ በገና ደርዳርያን እና መምህራን፣ ሰባኪያነ ወንጌል፣ ከተለያዩ ሀገራት የመጡ እንግዶች እና የበገና ወዳጆች የተገኙ ሲሆን ቀሲስ ብሥራት ሐለፎም መርሐግብሩን በጸሎት እና በቡራኬ አስጀምረውታል።
በመቀጠልም ተጋባዥ እንግዶች መዘክሩን በጎበኙበት ወቅት ስለስብስቡ ገለጻ ተደርጎላቸዋል። በዚህ መዘክር ውስጥ ቅዱስ ዳዊት በተለያዩ የቤተክርስቲያናችን ሠዓልያን ውስጥ የነበረውን መልክ የሚያስቃኘው ትዕይንት የመጀመርያው ሲሆን፣ እምብዛም የሚታወቁት እናት በገነኞችን የሚያስቃኘው ትዕይንት ደግሞ ሁለተኛው ነው። የመጨረሻው እና ሠፊው ትዕይንት ደግሞ በ1900ዎቹ ውስጥ የነበሩ በገነኞችን ታሪክ በከፊል የሚያሳየው ትዕይንት ነው።
በማስከተል በመካሻ መኮንን እና እሌኒ ፋሲል የበገና ዝማሬ የቀረበ ሲሆን ስለ አምባው አመሠራረት እና ጉዞ በአምባው ሥራ አስኪያጅ ምንተስኖት ተስፋዬ መግለጫ ተሰጥቷል።
በትውልድ ቅብብሎሽ የመጡ ነገሮችን ጠብቆ ማስጠበቅ የሁላችንም ታሪካዊና መንፈሳዊ ግዴታ ነው ያሉት ሊቀ ልሳናት መምህር ሲሳይ ደምሴ ሁሉ የሚሰምረው በንስሐ ሕይወት እና በቅዱስ ቁርባን ሲታጀብ እንደሆነ አጽኖት ሰጥተው መልዕክት አስተላልፈዋል። መርሐግብሩ ላይ በመገኘታቸው እና የተጀመረውን ሥራ በማየታቸውም እንደተደሰቱም ገልጠው ወደፊት ብዙ ሥራ እንደሚያስፈልግ ማሳሰቢያ ሰጥተዋል።
በገናን በሚመለከት ይህን የመሰለ ስብስብ አምጥቶ ማሳየት እና ለዚህ መብቃት ትልቅ በመሆኑ የተሰማቸውን ደስታ የገለጹት መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ የበገና ትውፊት በነበረበት ሁኔታ መቀጠል አለበት እንጂ መለወጥ የለበትም የሚል ታላቅ አደራንም ሰጥተው አባታችን የተሰኘውን ተወዳጅ ዝማሬአቸውን አሰምተዋል።
አምባ ሐዋዝ የፊታችን ሰኞ ሚያዚያ 12 ትምህርት መስጠት በይፋ የሚጀምር እንደመሆኑ ለምዝገባ ክፍት መደረጉም ተገልጿል።
በመጨረሻም መርሐግብሩን በቡራኬ ያስጀመሩት ቀሲስ ብሥራት ሐለፎም ከሁሉ በላይ እግዚአብሔርን ማወቅን ማስቀደም እንደሚያስፈልግ በማሳሰብ መርሐግብሩን በጸሎት ዘግተው አሰናብተዋል።
አምባ ሐዋዝ
ሚያዚያ 8፣ 2018 ዓ.ም